አምናለሁ አትቀሪም

አምናለሁ አትቀሪም

/በ ሃይማኖት ተካ/

የታደለ ድንጋይ በአምላክ ተቀድሶ ታቦት ያሳድራል፤
ስሙ ተቀይሮ እየተሳለምነው ከብሮ ያስከብራል፤
የረገጥነው አፈር የተደገፍነው ግንድ ልጅሽ ከወደደ፤
ዘግነን ተቀብተን ቆርጠንም አጭሰን መዳኛ ይሆናል
እሱ ከፈቀደ::

ርግበ ጸዓዳ ሀገረ ክርስቶስ ቤተ ሃይማኖቴ፤
የመማጸኛዬ ቃልና ቀለሜ የምታረቅብሽ ርቱዕ አንደበቴ::
ነያ ሠናይት ጎትተሽ ውሰጂኝ አቅርቢኝ ከደጁ
ነያ ዕፀ ሕይወት ከበሩ አዝልቂኝ አስዳሺኝ በእጁ::
እንደተራራቁት እንደኒያ ድንጋዮች እንደታነጹብሽ፤
እጠብቅሻለሁ አንድ እስክታደርጊኝ አማልደሽ ከልጅሽ::
አምናለሁ አትቀሪም. . .

እንደሚለመልም ሰም እሳት ሲያቀልጠው፤
በስምሽ ተጠርቶ ድንጋዩ ተስቦ በእጅ በታነጸው::
ከምሥጢር እንዳንጎድል በቤተ መቅደሱ ተሰብስበንበት፤
በተሠራልን ልክ አውቀን እንድንኖር እንድንበቃበት፤
ነይ እመብርሃን ቦዶነታችንን ፍቅርሽን ሙይበት::
አምናለሁ አትቀሪም::