“በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፡፡” (መዝ 64÷11)

“በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፡፡” (መዝ 64÷11)


የዘመናት ባለቤት ልዑል እግዚአብሔር ከዘመነ ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ዘመነ ቅዱስ ማቴዎስ አሸጋግሮ እንኳን ለአዲሱ ዓመት አደረሰን አደረሳችሁ፡፡ ከዓለም በፊት የነበረ ዓለምን ፈጥሮ የሚገዛ ዓለምንም አሳልፎ የሚኖር ዘመናትን የሚያመላልስ ደቂቃን በሰዓት፣ሰዓትን በዕለት፣ ዕለትን በወር፣ወርን በዓመት የሚጠቀልል ዓመታትንም የሚያቀዳጅ እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ እርሱ ግን ለዘለዓለም የማይለወጥ መጀመሪያም መጨረሻም የሌለው አልፋና ዖሜጋ ራሱ የሆነ የዘለዓለም አባት ነው፡፡ (ዮሐ 22÷13)

“አንተሰ አንተ ክመ ወዓመቲከኒ ዘኢየኃልቅ” (መዝ 101÷27) አንተ መቼም መቼ አንተ ነህ፤ ዘመንህም ከቶ አይፈጸምም ተብሎ እንደተጻፈ ፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር ዘመን የማይቆጠርለት ዘመናትን ለሰው ልጆች በምሕረቱ ዓመታትን እየባረከ ያቀዳጃል፡፡ የሰው ልጅ ከአባታችን ከአዳም ጀምሮ እስከ አሁን ብዙ ትውልድ እያለፈ ትውልድ እየተተካ ዘመናትም እያለፉ ዘመን እየተተካ ካለንበት ዘመን 2017 ዓመተ ምሕረት ላይ ደርሰናል፤እግዚአብሔር አምላካችን ፍጥረታትን በመግቦቱ ጠብቆ ተራሮችና ኮረብቶችን በዝናብ አጥግቦ ልምላሜን እንደዝናር እንዲታጠቁና አሸብርቀው ደስታን እንዲሞሉ አደረገ፤የሰው ልጅም በንስሐ ተመልሶ የለመለመ ሕይወትን ይኖር ዘንድ በቸርነቱ አዲስ ዓመትን አቀዳጀ፡፡ ስለሆነም በተሰጠን አዲስ ዓመት በኃጢአት የወደቅን ከኃጢአት በንስሐ ተመልሰን፤የተጣላን ታርቀን የተሰጠን የምሕረት ዓመት ነውና ቅዱስ ጳውሎስ በኤፌሶን መልእክቱ (ኤፌ 4÷23)“በአእምሯችሁ መንፈስ ታደሱ”እንዳለ የጽድቅን ሥራ ሠርተን በፍጹም ተለውጠን አዲስ ሰው መሆን ይጠበቅብናል፡፡ አዲስ ዓመት የተቀየረው ለሰው ልጆች ነውና የእግዚአብሔርን ምሕረት በማሰብ ራሳቸንን ለጽድቅ በማስገዛት በንስሐ ታጥበን የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ተቀብለን ለመንግሥቱ የተዘጋጀን የምንሆንበት ዓመት ያደርግልን ዘንድ የዘመናት ባለቤት የአምላካችን መልካም ፈቃዱ ይሁንልን፡፡