ገብር ኄር

ደብረ ዘይት

“ኢየሱስ ይህን ሰው ተኝቶ ባየ ጊዜ፥ እስከ አሁን ብዙ ዘመን እንዲሁ እንደ ነበረ አውቆ፡— ልትድን ትወዳለህን? አለው።” ዮሐ 5፥6

ምኩራብ

ቅድስት

ዘወረደ

“እኔ ነኝ በአንተ ልጠመቅ የሚገባኝ እንጂ አንተ እንዴት ወደ እኔ ትመጣለህ?” ማቴ. 3፥14-15

ቅዱስ ዮሐንስ በዮርዳኖስ ወንዝ አይሁዳውያንን ሲያጠምቅ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተራ ሰው መስሎ መጣ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ገርሞት “እኔ ነኝ በአንተ ልጠመቅ የሚገባኝ እንጂ አንተ እንዴት ወደ እኔ ትመጣለህ?” ማቴ. 3፥14-15 በማለት ማጥመቁን እምቢ አለ፡፡ ኢየሱስ ግን “አሁንስ ተው አትከልክለኝ የምጠይቅህን ጥምቀት ስጠኝ፡፡ ምክንያቱም ሕግን ሁሉ መፈጸም  ተገቢ ነው፡፡” ሲለው የጥምቀት ውኃ በራሱ አፈሰሰበት፡፡ ኢየሱስ ከተጠመቀ በኋላ ወደያው በራሱ ላይ መንፈስ ቅዱስ ወረደ፡፡ ሰማይም ተከፈተ “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው” ማቴ. 3፥17 የሚል ድምጽ ከሰማይ መጣ፡፡ ኢየሱስ የተጠመቀው ግዳጅ ስለነበረበት አይደለም፡፡ ሕግን ሁሉ መፈጸም እንዳለበት በተለይ ደግሞ ምስጢረ ጥምቀት ለደኀንነታችን የግድ አስፈላጊ መሆኑን ሊያስተምር ፈልጐ ነው፡፡ ኢየሱስ ለኒቆዲሞስ “ሰው ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ እንደገና ካልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት አይችልም” ዮሐንስ 3፡5 ሲል ተናገረው እንዲሁም “ወደ ዓለም ሙሉ ሄዳችሁ ወንጌልን ለሕዝብ ሁሉ ስበኩ በአብ፣ በወለድና በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቋቸው፡፡ ያመነና የተጠመቀ ይድናል ያላመነ ግን ይፈረድበታል” ማር. 16፡16

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ገና ከዮርዳኖስ ወንዝ ሳይወጣ እዚያው ቆሞ እያለ መንፈስ ቅዱስ በእርሱ ላይ ወረደ፡፡ “በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው” እያለ እግዚአብሔር አብ ተናገረ፡፡ ይህ ጥምቀት በሚቀበል በእያንዳንዱ ሰው ይደገማል፡፡ እኛ ጥምቀትን ስንቀበል መንፈስ ቅዱስ በማይታይ ሁኔታ በእኛ ላይ ይወርዳል፡፡ እግዚአብሔር ያን ጊዜ “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው” እያለ ተሰስቶ ይቀበለናል የላቀና የጠለቀ ደስታውን ይገልጣል፣ የእግዚአብሔር ልጆችና የመንግሥተ ሰማያት መራሾች ያደርገናል፣ በጥምቀት ጸጋ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከባርነት ወደ ነጻነትና ጽድቅ እንሻገራለን፣ የቅድስት ሥላሴ ማደሪያና ምድራዊ መኖሪያ እንሆናለን፡፡ ጥምቀት ስንት መንፈሳዊ ሀብትና ጸጋ እንደሁም ከፍ ያለ የእግዚአብሔር ልጆች ክብር ይሰጠናል፡፡ እኛም  ከማኅፀነ ዮርዳኖስ  ከአብራከ  መንፈስ  ቅዱስ ስለተወለድን ነው የቅድስት ሥላሴ ልጆች የሆነው::

ግን ምድራዊ ሀብት ጠንቀቅ ብለን ካልጠበቅነው ሊጠፋና ሳንጠቀምበት ሊቀር እንደሚችል እንዲሁም የጥምቀት መንፈሳዊ ሀብት ተግተንና ነቅተን ካልሰራንበት ጥቅም ሳይሰጠን ባክኖ ሊቀር ይችላል፡፡ ጥምቀት ስለተቀበልን ድነናል ብቁዎችም ሆነናል መንግሥተ ሰማያትን ወርሰናል ማለት አይደለም፡፡ ደኀንነታችን ፍጹም እንዲሆን መንግሥተ ሰማያት እንድንገባ በበኩላችን በደካማ አቅማችን በሚፈቅደው ያላሰለሰ ጥረትና ትግል ማድረግ አለብን፣ የደኀንነታችን መሠረት ልንቀጥለውና መልካም ፍሬ እስከሚሰጥ ድረስ ልናሳድገው እንዲሁም ግራና ቀኝ ሳንል በደኀንነት ጐዳና እንድንጓዝ ያስፈልገናል፡፡ ስለዚህ አንድ ጊዜ ጥምቀት ተቀብለናል፣ ተጠምቀናል ይበቃናል፣ አሁንስ ለዘለዓለም ድነናል ብለን ከመንፈሳዊ ጥረት ውጊያ ተግባር ማረፍና ማቋረጥ አይገባንም፡፡ በጥምቀት ጸጋ ተመርተን እንድንሄድና ኑሮአችን ከሕይወታችን አረማማድ ከመንፈስ ጥምቀት እንዲስማማ ማድረግ ይገባናል፡፡ ቅዱስ ያዕቆብ “እምነት ያለሥራ የሞተ ነው” ያዕቆብ 2፥26 እያለ ያስጠነቅቀናል፡፡

ቤተክርስቲያን ስንጠመቅ “በዘለዓለም ሕይወት ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመውረስ ከፈለግህ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ጠብቅ፣ እግዚአብሔር አምላክህን በፍጹም ልብህ ውደድ፣ ባለንጀራህንም እንደራስህ አድርገህ ውደድ፤ ሰይጣንና ሥራውን ሁሉ ካድ በኢየሱስ እመን” እያለች ታስጠነቅቀናለች፡፡ እኛም ደግሞ እክዳለሁ … አምናለሁ …” እያልን እንመልስላታለን፡፡ እንግዲህ ቃላችንን እንጠብቅ መሐላችንንና እምነታችንን ፍሬ አፍርተን በተግባር እናሳይ፡፡ ያን የጥምቀት ጸጋ በበለጠ ጥረት ኰትኩተን እናዳብር፡፡

መልካም የጥምቀት በዓል ይሁንልን፡፡ አሜን ።

“ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” ኢሳ 7÷14

++ ፈኑ እዴከ እምአርያም
አድኅነኒ ወባልሐኒ እማይ ብዙኅ
ወእምእዴሆሙ ለደቂቀ ነኪር መዝ ፻፵፫፥፯ ++

ትርጉም፦

እጅህን ከአርያም ላክ
ከብዙ ውኃም አድነኝ
ከባዕድ ልጆችም አድነኝ

ምሥጢር፦

ረድኤትህን ከአርያም ላክ አንድም ልጅህን በሥጋ ላክ ከብዙ ጦር/ሠራዊት አድነኝ አንድም ከፍትወታት እኩያት ከኃጣውእ ርኩሳት ከፍዳ ከመከራ ነፍስ ፈጽመህ አድነኝ ከነናምሩድ ከነሳኦል ልጆች እጅ አድነኝ አንድም ከዲያብሎስ ወገኖች ሥልጣን አድነኝ:: እጅ/ክንድ ከአካል ሳይለይ የወደቀ እንደሚያነሣ፤ የራቀ እንደሚያቀርብ፤ የቀረበ እንደሚያርቅ፤ የተበተነ እንደሚሰበስብ የወደቀ አዳምን አንሥቷል የራቀ አዳምን አቅርቧል የተበተነውን መንጋ ሰብስቧልና እጅህን ላክልን እያለ ዳዊት የተማኅፅኖ ጸሎት አቀረበ።


አንድም የሰው ኃይሉ በክንዱ እንዲታወቅ የአብም ኃይሉ በወልድ ታውቋልና እጅህን ላክ አለ።
አንድም ኃጥአንን ሑሩ እምኔየ ብሎ ያርቅበታልና ጻድቃንን ንዑ ኀቤየ ብሎ ያቀርብበታልና ፈኑ እዴከ አለ።

መጣ ስንልም የሌለበት ስፍራ ኖሮ ወዳልነበረበት ዓለም ወይም ቦታ መጣ ማለታችን አይደለም። ሁሉ በመሐል እጁ የተያዘ ነውና የሌለበት ስፍራ የለምና ካለበት ዓለም ወዳለበት ዓለም መጣ እንላለን።

በዘመናችን ካሉ ሊቃውንት አንዱ ሊቅ እንዲህ ብለዋል
“ሰው በያዘው ነገር ላይ መቀመጥ አይችልም በያዘው ዓለም ላይ መቀመጥ የታቸለው እግዚአብሔር ብቻ ነው” ሰማይ ዙፋኑ ምድር የእግሩ መረገጫ ሲሆኑ ተወስኖ ታይቷልና።

ምሥጢሩ የዚህን ያህል ጥልቅና ረቂቅ ከሆነ በምሥጢረ ሥጋዌ ዙሪያ አምላክ እንዴት ሰው እንደሆነ ሰውም እንዴት አምላክ እንደሆነ ተመራምሬ እደርሳለሁ ማለት የውቅያኖስን ውኃ በእንቁላል ቅርፊት ቀድቶ ለመጨረስ እንደመሞከር ነው።

የዕለቱ ወንጌል፦ ዮሐ ፩፥፵፬ – ፍጻሜ

ቅዳሴ፦  ዘእግዚእነ

ከወንጌሉ ንባብ በጥቂቱ፦

የቅዱስ ፊልጶስ ጥሪና ምስክርነቱ ጌታችን ፊልጶስን ተከለኝ ብሎ ካስከተለው በኋላ ያለመዘግየት ስለተከተለው ወይም እንዲከተለው ስለፈቀደለት አምላክ ለመመስከርና ሌሎችን እሱ ወደተጠራበት ለመጥራት ጊዜ አላባከነም። ሙሴ በኦሪት ነቢያትም በትንቢት መጽሐፍ የጻፉለትን የዮሴፍን ልጅ የናዝሬቱን ኢየሱስን አገኘው ብሎ ለናትናኤል ምስክርነቱን በመስጠት ወደዚህ ሕይወት እንዲመጣ ጠርቶታል።
እዚህ ላይ የዮሴፍ ልጅ የሚለው ኃይለ ቃል በትርጓሜያችን የተቃና መሆኑን ልብ ይሏል። አይሁድ ባለማወቅ የዮሴፍ ልጅ የሚሉት፤ ሙሴ በኦሪቱ የጻፈለት፤ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት፤ እኛም አምላክ ወልደ አምላክ ብለን የምናምንበት የናዝሬቱን ኢየሱስን አገኘው ብሎ ለናትናኤል እንደመሰከረለት ተብራርቷል። ዮሴፍ ስንኳን በገቢር በሐልዮ ይህን ነጥብ አያውቀውም። ይህም በመልአኩ ቃል ተረጋግጧል። “ይህ ሁሉ የሆነው ከእግዚአብሔር ዘንድ በነቢይ የተነገረው ይፈጸም ዘንድ ነው” በማለት ዮሴፍ የተጨነቀበትን ሐሳብ ሲያርቅለት እናያለን። ማቴ ፩፥፳፤


በነቢይ የተነገረውም “ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” የሚለው ነው።
የሚሰመርበት ነጥብ፦ “ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች” የሚለው ነው። ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በቀር በድንግልና የፀነሰች ፈጽማ የለችም አትኖርምም። ይህም ከሆነ ዮሴፍ አባት የተባለው ወይም ሊባል የቻለው አሳዳጊ በመሆኑ ብቻ እንደሆነ ንጹሕ ሕሊና ያለው ሰው የሚረዳው እውነት ነው። ስለ ዮሴፍ መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር “ጻድቅ ስለሆነ” በማለት ነው። ጻድቅ ከሆነ ደግሞ የእግዚአብሔርን ሥራ አይዳፈርም አይጋፋምም። በረድኤት የተገለጠባትን ደብረ ሲና እንኳ ማንም ሊነካት አልደፈረም። በኩነተ ሥጋ የተገለጠባትን አማናዊቷን ቤተ መቅደስ ጻድቅ ተብሎ የተገለጠው ዮሴፍ እንዴት ሊዳፈር ይችላል? ቴዎዶጦስ የተባለ ሊቅ ነገረ ሥጋዌን በምሳሌ ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል። “ወህየንተ እድ ዘዝየ ዘይለክዖ ለቃል በጽሒፍ አእምር በህየ ከመ እግዝእትነ ድንግል ማርያም ይእቲ ዘወለደቶ ለቃል በሥጋ” ብሏል። ወደአማርኛ ሲመለስም “በጽሕፈት ጊዜ ቃልን ስለሚጽፈው እዚህ ስላለ እጅ ፈንታ በወዲህ ቃልን በሥጋ የወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንደሆነች እወቅ” ማለት ነው። ሃይ አበው ፶፫፥፳
ሊቁ ይህን የተናገረበት ምክንያት፦
ከልብ የተገኘ ቃልን ለመጻፍ ብንፈልግ በልባችን ያለውን ቃል በሠሌዳ ስንቀርፀው ቃል አካላዊ በመሆን ይገለጣል። ይሁን እንጂ በጽሑፍ የተገለጠው ቃል በጽሑፍ ከመገለጡ በፊት በልብ ህልው እንደነበረ አካላዊ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስም በሥጋ ማርያም ከመገለጡ በፊት በአብ ህልው እንደነበረ ማስረጃ ነው። የአምላካችን ልደት በእንዲህ ዓይነት ምሥጢር የተከናወነ መሆኑን ብርዕና ቀለም ሆና ያላየነውን እግዚአብሔርን እንድናየው ያደረገችን እመቤታችን ድንግል ማርያም ናት ሲል ሊቁ ቴዎዶጦስ በምሳሌ አስተማረን።

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በድርሳኑ፦
“አንተሰ ኦ ብእሲ ኢታስተንዕስ መጠና ለሃይማኖት ቅድመ አዕይንቲከ – አንተ ሰው የሃይማኖትን መጠን በልቡናህ አታሳንስ አንድም አዋርደህ አትያት” ብሏል። ድር. ዘዮሐ አፈ ወርቅ ፱፥፺፭

ለእኛ ያልተረዳን ሁሉ ስሕተት፤ እኛ ልክ ነው ያልነው ሁሉ እውነት ሊሆን አይችልም። የእኛን ስሜት ብቻ ተከትለን በሄድን መጠን የሃይማኖታችንን ምሥጢር እያሳነስነው ልንሄድ እንችላለንና።

አዲስ ዓመት – ሐዲስ ሕይወት

ጳጉሜን ፭ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም

እንኳን ለዘመነ ማርቆስ አደረሰን!

ልዑል እግዚአብሔር በቸርነቱ ወቅቶችን ያፈራርቃል፤ ዝናብን ያዘንባል፤ ፀሐይን ያወጣል፡፡ ይህን ማድረጉ ለሰው ሁሉ ነው እንጂ በእርሱ ለሚያምኑ ብቻ አይደለም፡፡ ይህ ሁሉ ግን ለሰው ሁሉ ከእግዚአብሔር የተሰጠ (የሚሰጥ) መክሊት ነው፡፡ የጊዜያዊውን ፀሐይ መውጣት፤ ዝናቡን መዝነብ ተመልክቶ ዘለዓለማዊ የምትሆን የጽድቅ ፀሐይ እንድትወጣለት፤ አምላካዊት የምትሆን የምሕረቱ ዝናብም በሕይወቱ እንድዘንምለት በእውነት የሚናፍቅና ወደ እግዚአብሔር የሚቀርብ ሰው በተሰጡት መክሊቶች ያተረፈ ሰው ነው፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ዕድሜ ተሰጥቶት፤ የወቅቶች መፈራረቅ፤ የፀሐይ መውጣትና የዝናማት መዝነምን እንደ ሕይወቱ የመጨረሻ ግብ አድርጎ በምድር ላይ የሚኖር፤ ማለትም በዚህ ጊዜያዊ ዓለም የተዋጠ ሰው እግዚአብሔርን አያስብም፤ ጽድቁንም በእርሱም የሚገኘውን ሐዲስ ሕይወት አይናፍቅም፡፡ ይህ ደግሞ ከሕይወት መስመር መውጣት ነው፡፡ አዲስ ዓመት ሲመጣ የሕይወትን አዲስነት ካልያዝንበት አዲሱ ዓመት ጥቅሙ ምንድነው? ለዚህም ነው ከኀጢአት ዕርጅና ወጥተን አዲስ የምንሆንበትን ንስሐን ያስተማረንን ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅን በዓመቱ መጀመሪያ ላይ ማሰባችን፡፡ ሰው ለንስሐ የሚገባ ፍሬ የማያደርግ ከሆነ ዓመቱ ብቻውን እንዴት አዲስ ይሆናል? 

ክብርና ምስጋና ለእርሱ ይሁንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የመሆኑ ምክንያት ለሰው የጠፋበትን ሰውነት (ሰው መሆንን) ዳግም ለመስጠት ነው፡፡ ሐዲስ ሕይወትን ጸጋ አድርጎ ለመስጠት መድኅን ክርስቶስ በሥጋ ወደ እኛ መጣ፡፡ መጥቶም የመጀመሪያው ትምህርቱ ያደረገው ንስሐን ነው፡፡ ያለ ንስሐ ወደ እግዚአብሔር መቅረብ አይቻልምና፡፡ የሕይወት ባለቤት የሆነ እግዚአብሔር አዲስ ሕይወትን የሚሰጥ ወደ እርሱ በንስሐ ለቀረቡት ነውና፡፡ ይልቁንስ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን አሮጌውን ሰው ከሥራው ጋር በመተው አዲሱን ሰው (ክርስቶስን) በሃይማኖትና በምግባር ለሚለብሱት አዲስ ሕይወት ጸጋ ሆና ትሰጣዋለች (ቆላ. 3፥9)፡፡ አዲስ ዓመትን ስንታደል በሐዲስ ሕይወት ለመመላለስ መፈለግና መናፈቅ አለብን፡፡ በጥምቀት ከክርስቶስ ጋር ከተቀበርን ከክርስቶስ ጋር በሐዲስ ሕይወት እንደምንኖር ዳግመኛ ይህ የተወደደ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ያስተምረናል (ሮሜ 6፥4)፡፡

ዛሬ አዲስ ዓመት አድርገን የምናከብራት ቀን፤ በብሉይ ኪዳን የተቀደሰች ቀን መሆኗ የተነገረላት፤ እስራኤል መሥዋዕትን የሚያቀርቡባት፤ መለከት የሚነፋባት የተባረከች ቀን ናት፡፡ እስረኤል ይህችን ቀን ያከብሩ ዘንድ ከእግዚአብሔር ዘንድ ታዘዋል (ዘሌ 23፡ 24-25፤ ዘኁ 29፡ 1-2)፡፡ የምስጋና ዝማሬዎችም በዚህች ቀን ይቀርቡባታል፡፡

ለእኛ ለክርቲያኖችም ይህ ቀን እውነተኛውን ምስጋና የምናቀርብበት ዕለት ነው፡፡ ዘመናት የሚሰጡን ከእግዚአብሔር ጋር አንድ ሆነን እንድንኖርባቸው በመሆኑ አዲስ ዓመትን ስንታደል የምናተርፍበትን መክሊት የታደልን አድርገን መረዳት ይገባናል፡፡ ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብም መሠረታዊው ጉዳይ ንስሐን መያዝ ነው፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ እንደሚስተምረን የንስሐን ፍሬ ማድረግ ይገባናል፡፡ ለአይሁድ አብርሃም አባት አለን ብላችሁ እንደምትሉት አይደለም ብሎ አስተምሮ ነበር፡፡ ዛሬም እኛ ተጠምቀናል፤ ኦርቶዶክሳውያን ነን ማለታችን ብቻውን በቂ አይደለም፡፡ ይልቁንስ ፍቅርን ይዘን በንስሐ ወደ መድኅን ክርስቶስ ብንቀርብ ሕይወታችን በጸጋ እና በጣዕም የተመላች ትሆናለች፡፡ አምላካችን በአዲሱ ዓመት ወደ ሐዲስ ሕይወት ያስገባን ዘንድ ቸርነቱን ያድርግልን፡፡ አሜን!

ፍሬውን ለመብላት ሥሩን ውሃ ማጠጣት

/ሊቀ ጠበብት ማኅቶት የሻው/

> ፍሬውን ለመብላት ሥሩን ውሃ ማጠጣት

ይህ በምሳሌነት የቀረበ የአንድ ዕጽ /ዛፍ/ የእድገት ባህርይ ሲሆን ለሚሰጠው ፍሬና ጥቅም እውነተኛ አባባል ነው ። አንድ  ዛፍ አድጎ አንሰራፍቶ ጥሩ ፍሬ አፍርቶ ጥቅም ሊሰጥና ሊበላ የሚችለው ፣ ከምግብነት አልፎ በዛፍነቱም ለአዕዋፋት እና ለእንስሳት መጠለያ መከላከያ ሊሆን የሚችለው ቀጥ ብሎ አድጎ ሲፈለግ ለተለያየ አገልግሎትም እንዳደረጉት የሚሆነው ሥሩ ውሃ ሲጠጣ ነው ሉቃ 13፥8 ። በተጨማሪም የሚስማማውን ማዳበሪያ ፣ ልዩ ልዩ ማዳበሪያ ከሥሩ ሲያስታቅፉት ሲኮተኩቱትና ሲንከባከቡት ጥሩ ዛፍና ጥሩ ፍሬ ይወጣዋል ዮሐ 15፥1። ነገር ግን ችግኙ እንደተተከለ ምንም አይነት እንክብካቤ ካልተደረገለት ላያድግና ፈጽሞ ሊደርቅም ይችላል:: ምናልባት በተፈጥሮው ችግርን ተቋቁሞ ሊያድግ ቢሞክርም ይቀነጭራል እንጅ አያድግም:: ስሙም ዛፍ ሳይሆን ቁጥቋጦ ይባላል:: ቁጥቋጦ ደግሞ ለምንም አይሆንም። የደረሰ ሁሉ እንደፈለገ ይጎነትለዋል ፣ ይቆርጠዋል ረብ የለሽ ይሆናል። እንግዲህ ይሄ ለራሱ ለዛፉ የቀረበ እውነተኛ ታሪኩ ነው ። ምሳሌነቱ ወይም ንጽጽሩ ደግሞ ስለሕፃናት ወይም ስለሰው አስተዳደግ ነው ። ዛፍ ይተከላል ፣ያድጋል፣ይሞታል ለዚህ ነው ሳይንስ ዛፍ ሕይወት አለው እሚለው ። ሰውም ይወለዳል፣ያድጋል፣ይሞታል ክቡር የሆነው የሰው ልጅ በእናቱ ማኅጸን ከተቀረጸ ጀምሮ እንክብካቤ ይፈልጋል። ምክንያቱም በአዕምሮም በአካልም ለማደግ እንክብካቤ በመሆኑ በተለይም ተወልዶ በቋንቋ መናገር ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ልክ እንደዛፉ በጥሩ ሁኔታ አድጎ ሰው ለመሆን ሥሩን ውሃ ማጠጣት ነውና ከዛፉ እጅግ በተለየ መልኩ እንክብካቤ ያስፈልገዋል ።

ዛፍ ለራሱ ምግብ ብቻ ነው እሚፈልገው አያስብም ፣አይናገርም ፣አይሠራም ምንም ኃላፊነት የለበትም ሰው ግን ያስባል፣ይናገራል፣ይሠራል በዚህም የተነሳ ነገ ከነገ ወዲያ በሥጋዊም በመንፈሳዊም ህይወት አድጎ ሰው ብቻ ሳይሆን መልካም ሰው ፣ጥሩ ዜጋ፣ ቀና አመለካከት፣ በጥሩ እውቀት የተሞላ ሆኖ  ጥቅሙን ለማየት«ፍሬውን ለመብላት ሥሩን ውሃ ማጠጣት» ተገቢ ነው:: ወላጆች በልጆች አስተዳደግ ሂደት ይህን የማድረግ ኃላፊነት አለባቸው:: ልጆችን የመንግሥተ ሰማይ አርበኞች ፣የክርስቶስ ወታደሮች አድርገን በማሰልጠን በተሰማሩበት ህይወት ያለፍርሃት በፅኑ እምነት የእግዚአብሔርን መንግስት የሚመሰክሩ እንዲሆኑ ካረግናቸው ፍሬውን በላን ማለት ነው::

«ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታዎች ናቸው መዝ 127፥3» ይህን ውድ ስጦታ በሥጋዊም ሆነ በመንፈሳዊ ህይወት ኮትኩቶ ማሳደግ ያስፈልጋል:: በሥጋዊ አስተዳደግ በአሁኑ ሰዓት ብዙ ወላጅ ራሱን ጎድቶም ቢሆን የልጆቹን ፍላጎት ለማሟላት አስፈላጊውን ሁሉ ያደርጋል:: ልጆች ግን ይህን ውለታ ያውቁት ይሆን?  በተለይም በውጭው አለም ያለው የልጅ አስተዳደግ ዘይቤ /ሲስተም/ እጅግ የተለየና እንክብካቤውም የበዛ  ከመሆኑም በላይ፣ ልጆችን ጭራሽ ግዴለሽ እንዲሆኑ ሲያደርጋቸውና በፍቅር ፈንታ ለወላጆቻቸው ግድ ከማጣት አልፎም አንዳንዶቹም ጥላቻ ሲያሳድርባቸው ይስተዋላል:: ከዚህም አልፎ ጥቂት ነገር ከጎደለባቸው ወይንም አጥፍቶ ከተቆጡት ለፖሊስ ስለሚደውሉ  ወላጅም ፖሊስ መቶ እኔንም ከሚያሥረኝ ልጄንም ከሚቀማኝ ይልና እንደ አደራ /እንደሌላ ሰው/ ልጅ ተሳቆ አንጀቱ እያረረ የራሱ ልጅ እስከማይመስለው ድረስ ሲያጠፋ ማለትም ተጣሞ ሲያድግ እያየ ዝም ይላል።  እንደ ሀገራችን የዘመናዊ ተማሪ ቆይ 18 አመቴ ይድረስ እያለ ወላጁን ሲያስፈራራ ከመታየት አልፎም ልጆች በውጭው አለም እውነተኛ ምስክሮች ናቸው ተብሎ ይታመናል ። ስለዚህ ወላጅ «ከነገሩ ጦም እደሩ »ብሎ ችግሩ ቀጥሏል። ልጅን ሲያጠፋ እያረቁ፣ ጥሩ ሲሆን እየሳቁ፣ እያስተማሩ፣ እየመከሩ በቁምነገረኛነቱ እየኮሩ እንዲያድግ ማድረግ ነው::  ታዲያ አንድ ወላጅ አጥፍቶ ቢቆጣ ምንድነው ችግሩ ? ጉዳቱ ምን ይሆን? ወላጅ ልጁን እንደሰው ልጅ መሳቀቁ ለምን ? በሥጋዊ ህይወት ማሳደግ ሲባልኮ እንዲወፍርና የማይጠቅም ሥጋ ተሸክሞ እንዲቀጥል ፣ ስለሥጋ ብቻ እያሰበ  እንዲያድግ አይደለም::  ልጅን መቅጣት በጡት እሸት መብላትን በጥቅምት እንዲሉ አድጎ  ብዙ ለሚጠብቀው ነገር ሰዶ ማሳደድ  እንዳይሆን ስለቤተሰብ ፍቅር፣  ስለባህል፣ስለሃይማኖት ፣ስለ ሥነ-ምግባር እንደሙሴ እናት እንደ  ቆስጠንጢኖስ እናት አድርጎ ማሳደግ ያስፈልጋል::

መንፈሳዊ ህይወት

መንፈሳዊ ህይወት ሲባል ብቻውን መንፈሳዊ ህይወት ሳይሆን ሥጋዊ ህይወትን ይዞ  መንፈሳዊነትን መጨመር ማለት ነው፡፡ የዛሬን አያድርገውና ቀደም ሲል አባቶቻችን ንጉሥ ሁነው ካህን ካህን ሁነው ንጉሥ ነበሩ:: ንግሥት ሁነው ዳዊት ደጋሚ ቆራቢ አስቀዳሽ ጸሎተኛ ነበሩ:: በዚህም የተነሳ የተናገሩት ተደማጭነት እያገኘ ሀገርን አኩርተው ወገንን አክብረው በፈራሄ እግዚአብሔር በእዉነት ሲያስተዳድሩ ህዝቡም እጅግ በጣም ያከብራቸው ነበር። ምክንያቱ ደግሞ በሥጋዊም በመንፈሳዊም ህይወት በግብረ ገብ ተኮትኩተው በማደጋቸው ነበር። ይህን ተረት ተረት እሚመስል እውነት እንድናይ ከተፈለገ ዛሬም የሙሴን እናት ዮካብድን የመሰለች እናት ኦ .ዘኁ 26፥29 እንደ እስዋ ያለ እናት ካለች እንደ ሙሴ ያለ ጎበዝና ሃይማኖተኛ በሥጋዊም በመንፈሳዊ የተዋጣለት ጠንካራ ልጅ መውለድ ብቻ ሳይሆን ማሳደግም ይቻላል ፣ ሙሴ እናቱ የነገረችውን እንደጡት እየጠባ በሥጋዊ ሲጠነክር ግብጻዊውን ገሎ ወገኑን ከሞት ሲታደግ በዚሁ አድጎበት በኋላም ፈርኦንን ያህል ኃያል አስፈሪ ንጉሥ ሣይፈራ ወገኖቹን ከባርነት ቀንበር ነጻ አውጥቷል እግዚአብሔርም አግዞታል ።

  • በመንፈሳዊም ሲጠነክር 40 ቀን እና 40 ሌሊት በሲና ተራራ ጹሞ ጸልዮ ለማንም ፍጡር ያልተሰጠ ሽልማት ታቦተ ጽዮንን ከእግዚአብሔር እጅ ተቀብሏል ።
  • የንጉሥ ቆስጠንጢኖስ እናት ንግሥት ዕሌኒም በአሕዛብ እጅ ቁጥጥር ሥር ሁና ልጅ ብትወልድ ልጅዋን ለሃይማኖቱ ስለሀገሩ ስለፈራሄ እግዚአብሔር በሚገባ እያስተማረች አሳድጋዋለች። በሃይማኖት ቆራጥዋ እናት በገባችዉ ብጽዓት መሠረት በአካልም በመንፈስም ጠንክሮ ልጅዋ ለንግሥና ሲደርስላት በእርስዋ አሳሳቢነት ቢሆንም የእናቱን ትእዛዝ የሚቀበለዉ ቆስጠንጢኖስ የፈጣሪዉን የክርስቶስን ዕጸ መስቀል ለ6 ተከታታይ ወራት ቆፍሮ ያወጣ ያገኝ ታላቅ መሪ ነበር። እኛስ ? የኛ ልጆችስ ? እኛማ ሦስት ነገር እንኳን ማስተማር አቅቶናል የራሳችነን ቋንቋ ፣ባህል፣ ሃይማኖት እነዚህን ካስተማርን ሥነ-ምግባሩም በዚሁ ሊመጣ ይችላል ግን ስንቶቻችን ነን በነዚህ ጉዳዮች ከቤተሰባችን ጋር የምንግባባው ? ያልሆነ ምክንያት እየደረደርን ይደጉ ገና ናቸው፣ አናስጨንቃቸውም፣ የሀገሩ ህግ አይፈቅድም ወዘተ በማለት እንቆይና ገና ከፍ ሳይሉ ውሃ በብርጭቆ ቀድተህ አጠጣኝ ተብለው ቢታዘዙ እራስህ ተነስተህ ቀድተህ ጠጣ ሲሉ በዚህ መራገምና እራስን መውቀስ እንጀምራለን:: እንክብካቤ እንደጎደለው ቁጥቋጦ ተንጋዶ ስላደገ የት የተማረውን ያድርግ ቤተሰብ አላስተማረውማ:: እጅ ማስታጠብ፣ታላቅን ማክበር፣እግር ማጠብ አብርሐም ከነዘሩ የተባረከበት ይሄ ሥርዓት ነበር። ስለዚህ ለ8ኛው ሺህ ትውልድ ተጠያቂው የ8ኛው ሺህ ወላጅ ነው ። እስኪ ወገኖቸ ሁላችሁም በዓይነ ህሊናችሁ ወደኋላ ተመልከቱ እንዴት ነበር እናንተ ያደጋችሁት? አንዳንዱ ያልገባዉ ልጅማ እንደእኔ ሁኖ እንዲያድግ አልፈልግም ይላል። እንዲርበው እንዲጠማውኮ አይደለም የነገው ትልቅ ሰውነት የሚለካው ዛሬ ባሳደግንው ልክ ነው:: አንድ ሕጻን  በወላጆቹ፣በአካባቢው ማሕበረሰብ እና በትምህርት ቤት ተቀርጾ ያድጋል፤  ዋናዉ መሠረቱ ግን ቤት ውስጥ ነው:: ትልቁ ፈተናም ልጅ መውለዱ ሳይሆን ማሳደጉ ነው ። ቤተሰብ ትልቅ ተቋም ነው ።

ወላጆች ልጆቻችሁን እንደምትወዱ ምንም ጥርጥር የለውም:: ልጆችስ ወላጆቻችሁን ትወዳላችሁ? መልሱን ለራሳችሁ መልሱ:: በውጭው አለም ያለ ሁሉን ነገር ልመና ነው ብሉ፣ ጠጡ፣ ልበሱ፣ ተማሩ፣ ጎድሎበት ወላጁን በፍቅር የጠየቀው ነገር የለም በፍላጎት ያላደረጋው ነገር ስለሆነ ከላይ እንደተባለው ደንታቢስ ያደርገዋል የወላጅንም ዉለታ ከቁምነገር ካለመቁጠር አልፎም ከራሱ ፍላጎት ዉጭ ከሆነ ማን ውለደኝ ብሎሃል እስከማለት ይደርሳል። በዚህም የተነሳ የዘመኑ ልጆች ከወላጅ ይልቅ ገንዘብን፣ ከሰው ይልቅ ቁስ ነገርን የሚወዱት አሳዳጊ አጫዋቻቸዉ ሞባይል ስለሆነ እምታጎርሰው እናቱን እንኳን ቀና ብሎ ሳያይ እየተለመነ እየጎረሰ ስላደገ አይገነዘበውም:: ታዲያ በዚህ መልኩ ያደገ ልጅ ለየትኛዉ ቤተሰብ ለየትኛዉ አባትና እናቱ ለየትኛዉ እህት ወንድሙ ለየትኛዉ ዘመዱ ነው ፍቅር የሚያድርበት? በውነት እጅግ ያሳስባል፣እንቅልፍ ያሳጣል፣ ጉዳዩ ከባድ ነው::

መፍትሄዉ ምን ይሁን ?

  • ስልክ ይወዳሉ እያልን በር አንክፈት፣
  • እሚያስፈልገዉን ወላጅ ሊመርጥለት ይገባል፣
  • ቋንቋን ፣ባህልን፣ ሃይማኖትን ፣ሥርዓትን ፣ሥራንም ጭምር በአግባቡ ልናስተምራቸው ይገባል። 
  • በተቻለ መጠን ክጥሩ ጓደኛ ጋር እንዲውሉ ማድረግ «፡ከቅን ሰው ጋር ከዋልክ ቅን ትሆናለህ ከጠማማ ጋር ከዋልክ ጠማማ ሁነህ ትገኛለህ » መዝ 18- 25 ፣ አትሳቱ ክፉ ባልንጀርነት መልካሙን አመል ያጠፋዋል 1ኛ ቆሮ 15-33       
  • ለተወሰን ደቂቃም ቢሆን መንፈሳዊነትን ለማስርጽ ከልጆች ጋር መጸለይ፣ ምግብ ሲቀርብ ጸሎት አድርጎ /አባታችን ሆይ/ ብሎ መብላትን ማሳየት
  • ቅዱሳት ሥዕላትን በቤታችን አስቀምጠን መማጸኛ መለመኛ መጸለያ መማለጃ መሆናቸዉን ማስተማር/ በስእሉ ላይ በመንፈስ አድሮ እግዚአብሔር እንደሚሰማን መንገር፣ለሥእሉም ክብር መስጠትና ማሳየት
  • በተገኘው አጋጣሚ ሁልጊዜ ስለቤተ ክርስቲያን መወያየት፣ፍቅሩ እንዲያድርባቸው ተነሱ ብሎ የባህል ልብስን ለባብሶ ቤተ ክርስቲያን ሄደን እንሳለም ማለት ፣መሄድ አይወዱም እያልን አለማመካኘት ፣ ስለመስቀል መሳለም፣ ስለእምነት፣ ስድንግል ማርያም ክብርና አማላጅነት ፣ስለቅዱሳን ክብርና አማላጅነት፣እንዴት ማማተብ እንዳለብን ማሳየት፣ ሙዳየ ምጽዋት ማጠራቅምና መባ መስጠት ማሳየት ፣እንዲያደርጉ ማበረታታት ያስፈልጋል ለዚህ ሁሉ እንግዲህ የግድ ሰባኪ በየቤቱ አያስፈልግም። ቤተሰቡ በየቀኑ ትንሽ ትንሽ መጽሕፍ ቅዱስ በየተራ ማንበብ ፣  አይደለም ለነፍስ ጥቅም ለሥጋም ጥቅም ቢሆን ስንፍናን የምናበረታታ እንጀራ መቁረስ እንኳን የማናስተምር መሆን የለብንም::
  • በዚህ የግንኙነት ሰንሰለት ውስጥ እግዚአብሔር ሕጻናትን እንደሚወድ ማስረዳት እግዚአብሔር ሕጻናትን ይጠብቃልና
  • ሕጻናት ወደኔ ይመጡ ዘንድ አትከልክሏቸው ማቴ 19፥14
  • ማቴ18፥3 ካልተመለሳችሁ እንደሕጻናትም ካልሆናችሁ ወደመንግሥተ ሰማያት አትገቡም
  • እግዚአብሔር ሕጻናትን አስተዋዮች ያደርጋል መዝ 119፥130
  •  ከሕጻናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዝጋጀህ መዝ8፥2

ማጠቃለያ

በአግባቡ ጊዜና ትኩረት በመስጠት ከያዝናቸው ልጆቻችን መምህሮቻችን ይሆናሉ:: አለባበስንም ሥርዓትንም ሁሉንም ካሳየናቸው በደንብ ያኮሩናል በመንፈሳዊ ህይወት እንዴት እንደምናሳድጋቸው ልዩ ትኩረት መስጠት ግድ ይለናል:: ብንችል በተገኘው አጋጣሚ አስፈላጊውን መሥዋዕትነት እየከፈልን በኦን ላይንም ሆነ በአካል ከፊደል ጀምሮ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እንዲማሩ ማድረግ አለብን:: የአባቶቻችን ማንነት በዚህ የተመሠረተ ነውና ። « ጌታ ቸር መሆኑን ቀምሳችሁ እንደሆነ ለመዳን በእርሱ እንድታድጉ አሁን እንደተወለዱ ሕጻናት  ተንኮል የሌለበትን የቃልን ወተት ተመኙ » 1ጴጥ. 2፥2።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር